Wednesday 7 December 2016

የተማረ ገደለን

የኢትዮጵያ ወዳጅ ዶናልድ ሌቪን (ነፍሳቸውን ይማረው) ከ50 ዓመታት በፊት ጅምሮ ባህልንና ማንነትን የማያከብርና የሚክድ ህብረተሰባዊ ለውጥ አገር አፍራሽ ነው እያሉ ኢትዮጵያዊያንን ያስጠነቅቁ ነበር። ኃይለ ሥላሴ ወደ ምዕራብ አገር የላኳቸው ተማሪዎች በኢባህላዊ የሆነ  ከራስ ጋር የሚያጣላ ርዕዮት ዓለም ተነክረው ወደ አገራቸው ሲመለሱ በአስተሳሰባቸው ሰውዉን አስተንግጠዋል። አቶ ዶናልድ ሌቪን አንድ ያጋጠማቸውን እንደዚህ አስታወሱ ነበር፤ አንዱን «የተማረ» ምሁራንን እንደዚህ ብለው ጠየቁት «እንደምትመኘው የሶሽያሊስት አብዮት ቢካሄድ በሚሊዮን የሚቆጠር ህዝብ እንደሚሞቱ ታውቃለህን?» ይህ የተማረ ምህር «በ10 ሚሊዮንም ቢሞቱ ይህን ርዕዮት ዓለምን ለማድረስ ስለሆነ ያዋጣል» ብሎ መለሰላቸው። ከራስ ባህል፤ ወግ፤ ትውፊት፤ ምንጭና ማንነት መራቅ እንደዚህ አይነቱን ቅዠታዊ አስተሳሰብ ነው የሚያመጣው።

ዛሬም ይህ አይነት የቀለም ትምህርት አምልኮ ለኢትዮጵያ ዋናው አጥቂና ጠላት ነው። የምዕራብ ዘመናዊ የቀለም ትምህርት በአገራችን እንደ ጣዎት እንደሚመለክ የሚገልጸው በኃይለ ሥላሴ ዘመን የተሰየመው አባባል «የተማረ ይግደለኝ» ነው። ይህ ዛሬም በኢትዮጵያዊያን ጭንቅላት ይንጸባረቃል። ፖለቲካችንን ካየን አብዛኛው የሚንጸባረቁት ሃሳቦችና አስተያየቶች ከኢትዮጵያ ውጭ የመነጩ ናቸው። የኛ ምሁራኖች እነዚህ ሃሳቦችን እየሰገዱላቸው ኢትዮጵያን ወደ እኒዝህ ርዕዮት አለምን ማስተካከል ይፈልጋሉ። ቢያንስ መደረግ የነበረበት እነዚህን ርዕዮት ዓለሞችን ለኢትዮጵያ እንዲሆኑ ማስተካከል።

ይህ አቋሜን የሚደግፉ አንዳንድ ማስረጃዎች እንመልከት። በመጀምርያ ወደ ኋላ ሄደን የኃይለ ሥላሴ መንግስትን ተመልስን እንመልከት። የዛን ጊዜ ውጤቶች ዛሬ ከፍተኛ ሚና እየተጫወቱ ስለሆነ። በሳቸው መንግስት ዘመነ የምዕራብ «ዘመናዊ» ትምህርት በኢትዮጵያ ውስጥ ተስፋፋ። ተማሪዎች በሞላ ጎደል አለምንም መበረዝ ቀጥታ የምዕራብ ትምህርት ነበር የሚማሩት። ስለአገራቸው ጥቂት ውይም ምንም ነገር ሳይማሩ ይመረቁ ነበር። ለምሳሌ ስለ ዓለም ዙርያ መልክአምድር ተምረው ስለኢትዮጵያ መልክአምድር ምንም አያቁም ነበር! ስለራሳቸው ታሪክ፤ ትውፊት፤ ባህልና ሃይማንቶ አይማሩም ነበር። ሳይታወቅ ግራ የገባው ከፊል ኢትዮጵያዊ ከፊል ፈረንጅ የሆነ ትውልድ ተወለደ። የዝቅተኛ መንፈስ ያደረበት ትውለድ ተፈጠሪ። ሳያውቀው እራሱን የሚንቅና የሚጠላም ትውልድ ተፈጠረ። ግን ከዚህ ትውልድ ልጆች መካከል ግማሾቹ ኢትዮጵያዊነታቸው ቢሸረሸርም ለኃይለ ሥላሴ ታማኝ ነበሩ በሳቸውም «የዘመናዊ ስልጣኔ እቅድ» ይስማሙ ነበር። ሌሎቻቸው ግን እንኳን ታማኝ ለመሆን ጠላት ሆነው ተገኙ። አገሪቷን ያስከወሰ አብዮትን አስነሱ። ሁላችንም እንደምናውቀው ይህ አብዮት በአገራችን አስፈላጊ የሆኑ ለውጦችና መስተካከሎች ከማምጣት ፋንታ በጸረ ኢትዮጵያ የሆነውን በምዕራባዊያኑ ርዕዮት ዓለም በኮምዩኒዝም ስር አገራችንን እንድትወድቅ አደረጋት።

በደርግ ዘመነ መንግስት ደግሞ አብዛኛው የኢትዮጵያ የፖለቲካ ንቅናቀዎች የጸረ ኢትዮጵያ አቋምና ርዕዮት ዓለም ይዘው ነበር የሚራመዱት። ጸረ ሃይማኖት ነበሩ። ጸረ ባህልና ጸረ ትውፊት ነበሩ። እርግጥ በዛን ዘመን ሙዚቃ ጭፈራ ወዘተ «ትስፋፍቷል»። ግን የተስፋፋው በምዕራባዊያን አመለካከት ዘንድ ነው - ስር የሰደደ የማንነት የሆነ ሳይሆን እንደ ልብስ ከላይ የሚለበስ ወይም እንደ ቴአትር የሚታይ ነበር። በመጀመርያ ኮምዩኒስት ነን፤ ግን እስክስታ የምንጨፍር ኮምዩኒስት ነን! በጠቅላላ አብዛኛው ፖለቲከኞችና ምሁራንም የኢትዮጵያ ማንነት መቀየር አለበት ብለው የሚያምኑ ነበሩ።

በኢህአዴግ ዘመን ይህ ወደ ውጫዊ አመለካከት ማድላት ወደ ጸንፍ ደረሰ። በሶሺአሊዝም የተሞላ በጎሳ የተመሰረተ ጸንፈኛ ህገ መንግስት በኢትዮጵያ ተጫነባት። ይህ ክስተት ከኢትዮጵያዊ «የተማረ» ኃይል በተደጋጋሚ የሚታይ አንድ ጸባይን በደምብ ያብራራል። ይህ ጸባይ ጸንፈኝነት ነው። የኢትዮጵያ መሰረታዊ ችግር የብሄር እኩልነት ነው ብሎ ቢታመንም ቋንቋ፤ ባህል፤ መልክአ ምድር፤ ጎሳም የሚያካተት ግን ለዘብተኛ የሆነ ህገ መንግስት ሊመሰረት ይቻል ነበር። ግን ያኔ የነበሩት ኃይሎች ጸንፍ ካልያዝን አሉ! በምድረ ዓለም ታይቶ የማይታውቅ አይነት ህገ መንግስት - ከሶሺያሊስት በላይ ሶሺያሊስት የሚያሰኝ ህገ መንግስት ካልደነገግን አሉ። ጭራሽ ከደቡብ አፍሪካ በቀር የሌለውን ጎሳ በመታወቅያ ጀመሩ! ሁላችንም እንደምናውቀው እስካሁን ይህ መርዝ ነው እያሳመመን ያለው።

ይህ ሁሉ ሆኖ የአገራችን ገዥም ተቃዋሚም ፖለቲከኞችና ምሁራን አሁንም ውጫዊ በተለይ ምእራባዊ አመለካከት ነው ያላቸው። ገዝ ፓርቲ «ዘመናዊነት» የሚባለው አመለካከት ነው ያለው። ሃይማኖት ኋላ ቀር ነው። እግዚአብሔር ሳይሆን ሰው ነው የዓለም ቁንጮ። ባህል፤ ትውፊትና ወግ ውሸት ናቸው። ህዝብ ባህልን ትቶ ወደዚህ አይህነት አመለካከት እስኪ ገባ ድረስ እንደ ያላደገ ህጻን ነውና እኛ ስልጣን ተቆጣጥረን ልናሳድገው ይገባል። ካደገ በኋላ፤ ማለት እንደኛ የ«ዘመናዊ» አስተሳሰብ ካደረበት በኋላ - ስልጣናችንን እንለቃለን። በሌላ አባባል ኢትዮጵያዊነቱን አርግፎ ከኛ ይበልጥ «ያደጉትንና የሰለጠኑትን» ምእራባዊያን ከመሰለ በኋላ ነው ሰው የሚሆነው። ይህ ራስን ማንነትን መጥላት ካልሆነ ምንድነው?

ተቃዋሚው ደግሞ እንደ አሜሪካ ወይም እንደ አውሮፓ እንሁን ነው! (በጅምላ እየተናገርኩኝ ስለሆነ ይቅርታ።) የኢትዮጵያዊነት ራዕይ የለውም። እርግጥ አንዳንድ ጥሩ የሆነ ሃሳቦች እንደ ገዳ አሰራር አጥንቶ በተወሰነ መጠቅም ተነስተዋል። አንዳንዱም ደፋር የንጉሳዊ አስተዳደር (በወግ ደረጃ ብቻ ቢሆንም) ይመለስ የሚሉ አሉ። እነዚህ ሃሳቦች በርካታ ውይይትና ክትትል ያስፈልጋቸዋል ከነዚህ አይነቱ ባህላዊ መንገድ ነውና የአገራችን ውበት የሚመለሰው።

በብዙሃኑ ደረጃ ደግሞ ቤተሰብ ልጁን የምእራባዊ ባህልና ቋንቋ ለማስተማር ይሯሯጣል! ለልጁ ከቀለም ትህምሕርት በላይ በዚህ ዓለም ምንም የለም የሚል መልክት ነው ደጋግሞ የሚያስተላልፍለው። ልጁም የቀለም ትምሕርትን ጣኦት አድርጎታል። ከዛ በኋላ የልጁ አኗኗር ግራ የገባው ሲሆን፤ ትምሕርትና ስራ አለው ግን በሌላው ንሩው ያልተረገጋ መሰረተ ቢስ የሆነ ሲሆን - ወላጅ ግራ ይገባዋል። የዛሬው ትውልድ እንደዚህ ነው እንደዛ ነው ብሎ ያማርራል። ታድያ ባህሉን ያልወረሰ ሰው ሁልጊዜ ኑሮው እንደሚናወጥ አናውቅምን?

በትህትና ባይመስልም ግን የትህትና ምክሬ እንደዚህ ነው። በመጀመርያ የዘመናዊ ትምህርት ምን ያህል ጸረ ባህል፤ ጸረ ትውፊት፤ ጸረ ማንነት፤ ጸረ ኢትዮጵያ እንደሆነ እንረዳ። ሞያ፤ ሳየንስና ቴክኖሎጊ ችግር የለውም ከጥንትም የነበሩ ዘርፎች ናችሀው ከምንምም ጋር አይጋጭም። አደገኛው ግን «ዘመናዊነት» የሚባለው ርዕዮት ዓለም ነው። ቅድም የጠቀስኩት ጸረ ሃይማኖትና ጸረ ባህል የሆነ አስተሳሰብን እንደ መርፌ ይወጋል። ይህን አውቀን ስንዴውን ከንክርዳዱን መለየት አለብን። ጠቃሚውን ትምህርት እየተማርን ጎጂውን እራሳችንን እንድንጠላ የሚያደርገውን ለይተን አውቀን እንተው። የምንማረውን በባህልና ሃይማኖታችን መነጽር ወይም አመለካከት እንማረው። ለልጆቻችንም እንደዚሁ።

ይህ ነው ምክሬ። ዶናልድ ሌቪን እንዳሉት - ክሁሉ ጥቅሳቸው ይህን ነው እጅግ የምወደው - "The vitality of a people springs from feeling at home in its culture and from a sense of kinship with its past. The negation of all those sentiments acquired in childhood leaves man adrift, a prey to random images and destructive impulses…" ከኔ የምትሻሉት ተርጉሙት!

No comments:

Post a Comment

ለሀሳብዎ አመሰግናለሁ!